Friday 14 November 2014

አዲሱ የመኢአድ አመራር ከሌሎች ፓርቲዎች ጋር የተጀመረው ግንኙነት እንደሚያስቀጥል አስታወቀ.

• የፓርቲውን ማህተም ተሰርቄያለሁ ብሏል
aeupዛሬ ህዳር 4/2007 ዓ.ም በፓርቲው ዋና ጽፈት ቤት መግለጫ የሰጠው የመኢአድ አዲሱ አመራር ከመኢአድ ጋር ተመሳሳይ ፕሮግራም ካላቸውና ከሌሎቹም የፖለቲካ ድርጅቶች ጋር ከአሁን ቀደም አብሮ ለመስራት የተጀመረውን እንቅስቃሴ እንደሚያስቀጥል አስታውቋል፡፡
በ2003 ዓ.ም ከታህሳስ 15-17 ድረስ አይቤክ ሆቴል ጠቅላላ ጉባኤ ከተካሄደ በኋላ በፓርቲው አመራሮች መካከል ችግር እንደነበር የገለጸው አዲሱ አመራር ከዛ በኋላ አቶ አበባው መሃሪ ፕሬዝደንት የሆኑበት አካሄድ ትክክል እንዳልነበር፤ለአራት አመት ያህል በሁለቱ ቡድን መካከል የነበረው አለመግባባት በእርቅ እንደተቋጨና አቶ አበባው ኃላፊነታቸውን በፈቃዳቸው እንደለቀቁ የጻፉትን ደብዳቤ ዋቢ አድርጎ ገልጾአል፡፡ በመሆኑም የፓርቲው አባላትና ደጋፊዎች ያለ ምንም ገደብ ወደ መኢአድ ጽ/ቤት መምጣት ይችላሉ ሲል ጥሪውን አስተላልፏል፡፡
በአንጻሩ አዲሱ አመራር በህገ ወጥ መንገድ ነው ወደ ስልጣን የመጣው በሚል ቅር የተሰኙ የፓርቲው አመራሮችና አባላት ዛሬ ከሰዓት መግለጫ እንደሚሰጡ ተሰምቷል፡፡ ጉዳዩን ለማጣራት አቶ አበባው መሃሪ ጋር በተደጋጋሚ ብንደውልም የእጅ ስልካቸውን ሊያነሱ ባለመቻላቸው ሀሳባቸውን ማጠቃለል አልቻልንም፡፡
በሌላ በኩል አዲስ አመራር ማህተሙ አዲሱ አመራር ከመምጣቱ በፊት ፓርቲው ውስጥ በነበሩትና በአዲሱ አመራር ጋር ባልተስማሙ አካላት እንደተሰረቀ አስታውቋል፡፡ ‹‹ማህተሙ ከዚህ ቤት በነበሩ ሰዎች ተሰርቋል፡፡ ይህን ጉዳይ በወቅቱ ለፖሊስ አመልክተናል፡፡ በፓርቲው ማህተም እኛ የማናምንበትና ህገ ወጥ ነገር ቢሰራበት ተጠያቂ የሚሆኑት እነሱ ናቸው፡፡›› ሲሉ አዲሱ የፓርቲው ፕሬዝደንት አቶ ማሙሸት አማረ ገልጸዋል፡፡

No comments:

Post a Comment