Wednesday 12 November 2014

የፕሬዚዳንቱ ልዩ አማካሪ ተነሱ.

የፕሬዚዳንት ሙላቱ ተሾመ (ዶ/ር) ልዩ አማካሪ አቶ አሰፋ ከሲቶ ተነሱ፡፡ አቶ አሰፋ የተነሱት በጠቅላይ ሚኒስትር ኃይለ ማርያም ደሳለኝ ፊርማ በተጻፈ ደብዳቤ ነው፡፡ በአቶ ኃይለ ማርያም ፊርማ የወጣው ደብዳቤ፣ አቶ አሰፋ ከኃላፊነት የተነሱበትን ምክንያት ያልጠቀሰ ሲሆን፣ አቶ አሰፋም በምን ምክንያት እንደተነሱ እንዳላወቁ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
አቶ አሰፋ ከሲቶ
አቶ አሰፋ ከሲቶ
‹‹ወደፊት የሚተገበሩ አዳዲስ ፕሮግራሞችን እየቀረፅኩ ነበር፤›› በማለት ከኃላፊነት መነሳታቸው ያላሰቡትና ያልጠበቁት እንደሆነ አቶ አሰፋ ለሪፖርተር ገልጸዋል፡፡
ደብዳቤው በጥቅሉ፣ አቶ አሰፋ ከኅዳር 2001 ዓ.ም. ጀምሮ የፕሬዚዳንቱ ልዩ አማካሪ በመሆን ላበረከቱት አስተዋጽኦ ምስጋናውን ገልጿል፡፡
በሥራ አፈጻጸምም ሆነ በሙስና እንዳልተገመገሙ አቶ አሰፋ ለሪፖርተር ገልጸው፣ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስቴር አዲስ የሥራ መደብ እንዲሰጣቸው ደብዳቤ መጻፉን ተናግረዋል፡፡
የሸካ ዞን፣ የኪ ወረዳ፣ የደቡብ ክልል ምክር ቤት ተመራጭ የነበሩት አቶ አሰፋ፣ የክልሉ ፀረ ሙስና ምክትል ኮሚሽነርና የደቡብ ፍትሕ ቢሮ ኃላፊ ሆነው ሠርተዋል፡፡
ከዚህ በተጨማሪም ለአምስት ዓመታት የሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ የሕግ መምህር ሆነው ሠርተዋል፡፡ አቶ አሰፋ የፕሬዚዳንቱ ልዩ አማካሪ ከመሆናቸው በፊት፣ የፍትሕ ሚኒስትር ሆነውም ሠርተዋል፡፡
አቶ አሰፋ የፍትሕ ሚኒስቴርን ለሦስት ዓመታት ከመሩ በኋላ ከቦታው ተነስተው የፕሬዚዳንቱ ልዩ አማካሪ ሆነው ተሰይመዋል፡፡
አቶ አሰፋ ላለፉት ስድስት ዓመታት የቀድሞውን ፕሬዚዳንት አቶ ግርማ ወልደ ጊዮርጊስንና በቅርቡ ፕሬዚዳንት ሆነው የተሰየሙትን ዶ/ር ሙላቱ ተሾመን ሲያማክሩ ቆይተዋል፡፡

No comments:

Post a Comment