Wednesday 19 November 2014

ባለፈው ወር ብቻ 5,000 ኤርትራውያን ስደተኞች ወደ ኢትዮጵያ ገብተዋል ተባለ

4da4c0c59ba52ecd40d2cc0712906e69_L
አገራቸውን ለቀው ወደ ጎረቤት አገሮችና ወደ አውሮፓ የሚፈልሱት ኤርትራውያን ስደተኞች በፍጥነት መጨመሩን ቀጥሎ ባለፈው የጥቅምት ወር ብቻ ከ5,000 በላይ የሚሆኑ ኤርትራውያን ድንበር አቋርጠው ወደ ኢትዮጵያ መግባታቸውን የተባበሩት መንግሥታት የስደተኞች ከፍተኛ ኮሚሽን አስታወቀ፡፡
ኅዳር 8 ቀን 2007 ዓ.ም. ከወደ ጄኔቫ የወጣው የኮሚሽኑ ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ ባለፈው ወር በኢትዮጵያ መጠለያ ፈልገው የመጡት 5,000 ስደተኞች ባለፈው ዓመት በተመሳሳይ ወቅት ከነበረው አጠቃላይ ቁጥር በ3,000 ጭማሪ አለው፡፡
እንደ ኮሚሽኑ ሪፖርት፣ ከአጠቃላይ ስደተኞቹ 90 ከመቶ የሚሆኑት ወጣቶች ሲሆኑ፣ በ18 እና 20 ዓመት የዕድሜ ክልል ውስጥ እንደሆኑም አትቷል፡፡ በተጨማሪም 78 ከመቶ የሚሆኑት ሕፃናትና ታዳጊ ኤርትራውያን ብቻቸውን ያለምንም አጋዥ ብዙ ርቀት ተጉዘው ድንበር በማቋረጥ ወደ ኢትዮጵያ እየገቡ መሆኑንም ሪፖርቱ አካቷል፡፡
የኮሚሽኑ ሪፖርት እንደሚያሳየው፣ በዓመቱ ወደ አውሮፓ የሚፈልሱ ኤርትራውያን ቁጥር በፍጥነት እያሻቀበና አሳሳቢነቱ እየተጠናከረ መጥቷል፡፡
እ.ኤ.አ. በ2014 የመጀመሪያ አሥር ወራቶች ብቻ የኤርትራውያን ስደተኞች ቁጥር በሁለት እጥፍ ያደገ ሲሆን፣ 37,000 ኤርትራውያን ወደ አውሮፓ መጉረፍቸውንና ባለፈው ዓመት ተመሳሳይ ወቅት ከነበረው 13,000 በሁለት እጥፍ መመንደጉን ሪፖርቱ አመልክቷል፡፡
እንደ ኮሚሽኑ ሪፖርት፣ በአሁኑ ወቅት 216,000 ኤርትራውያን ስደተኞች በኢትዮጵያና በሱዳን ተጠልለዋል፡፡
በተለይ እ.ኤ.አ. ከ2002 ጀምሮ ኤርትራውያን ወደ ኢትዮጵያ መጉረፍ የጀመሩ ሲሆን፣ አገሪቷ ውስጥ ያለው አገዛዝን በተለይ የአስገዳጅ የውትድርና አገልግሎትን ሸሽተው የሚጓዙበት ዋነኛ ምክንያት እንደሆነም የመንግሥታቱ ድርጅት ሪፖርት ጠቁሟል፡፡

No comments:

Post a Comment