Monday 27 October 2014

አማን ሄደቶ ቄረንሶ:- ተስፋዬ ገ/አብና የፓንዶራው ሳጥን — ክፍል አንድና ክፍል ሁለት

በአማን ሄደቶ ቄረንሶ*
ክፍል አንድ
እንደ መግቢያ
“ተውን አትቀስቅሱን አትንኩን በነገር፡
እኛም ትኋን በልቶን አልተኛንም ነበር።”
(ስንኙን ያገኘሁት ገጣሚው ካልተገለጸው የአማርኛ ግጥም ሲሆን የአጠቃላዩን ሃተታ ይዘት ተሸክሟል ብዬ እገምታለሁ። ወደ በኋላ እንመጣበታለን። እግረ መንገዴን፡ ማለት የምፈልገው ግን፡ በአማርኛ ስጽፍ የሚያስቅ ስህተት ከሰራሁ እንድትስቁ ፈቅጄላችኋለሁ፤ ሳቁ። ተገኝቶ ነው። ከሁለት ቀናት በፊት በማህበራዊ ድህረ ገጾች ያተምኩትን ይህንን ጽሁፍ ትንሽ አስተካክዬ ነው የላኩት። እንቀጥል።
አንዳንዴ ከጓደኞቼ ጋር ስንገናኝ ስለ ተስፋዬ ገብረአብ ስራዎች አንስተን ማውጋት የተለመደ ነው። ከኦሮሞ ህዝብ አንጻር ስለ ጻፋቸው ስለ እነ የቡርቃ ዝምታ፡ ስለ ዳንገጎ /Dhangaggoo/ ፈረሶች፡ ስለ አቶ ደራራ ከፈኒ፡ ስለ ኢብሳ ገዳ፡ ስለ ታሰረው አንበሳ፡ ስለ ቀዌሳ አመጽ፡ ስለ የሻምቡ ንጉስ፡ ስለ ሮሮ እና ይቅርታ፡ ስለ ቦረና የስልጣኔ ዋሻነት እና ሌሎችም …
አንድ ቀን በ “የቡርቃ ዝምታ” እና በ “ጫልቱ እንደ ሄለን” በኢትዮ ብቸኛ ልጆች ስለደረሰበት እርግማን፡ ውግዘት፡ ስድብና ስም ማጥፋት አንስተን ስናወራ የሰሙን አንድ የኦሮሞ አዛውንት ሲያዳምጡ ከቆዩ በኋላ “ተስፋዬ ማለት ማነው? ለምንስ ይወገዛል?” ብለው ይጠይቁናል። ስናወራ የነበረውን ደገምንላቸው። ስለማንነቱ ብቻም ሳይሆን ስለ ውልደቱና እድገቱም ነገርናቸው። አዳምጠውን ከጨረሱ በኋላ “እንግዲያውስ ተስፋዬ ምንም አልሰራም” አሉ። “እንዴት?” አልናቸው። “እንዲህ መሆኑ ካልቀረ ትልቁን ሳጥን ነው መክፈት የነበረበት” አሉን። ትልቁ ሳጥን የትኛው እንደሆነም ጠየቅናቸው። “ምን ማለታችሁ ነው?” ብለው ጀመሩ። “ተስፋዬ እኮ የትልቁን ሳጥን ቁልፍ ነካካው እንጂ አልከፈተውም። እነዚህ ሰዎች የሚበርድላቸው እነሱ በሚያቁት ቋንቋ ትልቁ ሳጥን ሲከፈት ብቻ ነው።” አሉን። ከዚያ የኦሮሞ አዛውንት ከተለየን በኋላ ቤት ገብቼ “የተነካካው የሳጥኑ ቁልፍ” ብዬ ብጫቂ ወረቀት ላይ ጻፍኩት።
በተፈጥሮዬ (የአማርኛን ጨምሮ) የማንኛውም ቋንቋ የስነጽሁፍ ውበት ይማርከኛል። በኦሮምኛዬ አሳምሬ እጽፋለሁ። አንድ ሁለት ልቦለድ መጽሃፍቶችም አሉኝ። አማርኛን ግን አነባለሁ እንጂ ደፍሬ ብዙ አልጽፍበትም። እፈራለሁ። በልጅነቴ “ሀ ሁ” ቆጠራ ላይ የመጀመሪያው “በ” እና አራተኛውን “ባ” እንዲሁም “ቢ” እና “ብ” ን ለይቶ መጥራት መከራ ነበር። በዚህም መገረፌን አልረሳም። አንደኛ ክፍል እያለን ነበር። አንድ ቀን መምህሩ ለተወሰኑ ቀናት ፊደል ካስቆጠረን በኋላ ፊደል መለየታችንን ሊያውቅ ፈልጎ አንድ በአንድ ይጠይቀን ጀመር። የተወሰኑ ልጆች እሱን ተከትለው እንዲሉ ነገራቸው። በሁሉም ደስተኛ ባይሆንም እኔ ጋ ደረሰ። ተከትዬው እንድል ነገረኝ። “በ” ብሎ ጀመረ። “ባ” አልኩት። እንዳላስተካከልኩት እየነገረኝ “በ በል” ሲለኝ አሁንም ደግሜ “ባ” አልኩት። አሁንም ተከትዬው እንድደግም ነገረኝ። “በ” ሲለኝ አሁን ቀይሬ “ቤ” አልኩት። ሳስቸግረው ተናዶ “ባ… ! ቤ… !” እያለ ከፎገረኝ በኋላ አርጩሜ ሊያስመጣ አንዱን ልጅ ላከ። አርጩሜውም መጣ። ስራውን ሰራ። በርግጥ “በ” ን ብቻ ሳይሆን “ብ” ንም ለመጥራት ተመሳሳይ መከራ ነበር ያየሁት። እኔ ብቻ ሳልሆን ኦሮምኛ አፍ መፍቻችን የሆነ ሁሉ “ብ” ስንባል “ቢ” ነበር የምንለው። ኋላ ላይ አድጌ፡ የዚያ ሁሉ ችግር ምንጭ በቋንቋዎች መሃል ያለው የድምጾች ልዩነት እንጂ የኛ ችግር የነበረ አለመሆኑን ስረዳ በነዚያ መምህራን በጣም ነበር ያዘንኩት።
በግእዝ ፊደል ቆጠራ “ግእዝ” የሚባሉ የመጀመሪያ እና ካልተሳሳትኩ “ሳድስ” የሚባሉ ስድስተኛ ድምጾች በኦሮምኛ ቋንቋ ድምጽ የሉም። በምሳሌ ለማስቀመጥ “ባ” እንጂ “በ” ድምጽ “ላ” እንጂ “ለ”፡ “ማ” እንጂ “መ” ድምጾች በኦሮምኛ የሉም። በተጨማሪም “ቢ” እንጂ “ብ” ድምጽ፡ “ሊ” እንጂ “ል” ፡ “ሲ” እንጂ “ስ” ድምጾች የሉም። እናም ኦሮምኛ ተናጋሪዎች እነዚህን ድምጾች ለመጥራት ይቸገራሉ። የግእዝ ፊደል ለኦሮምኛና አብዛኛዎቹ ኩሽ ህዝቦች ቋንቋዎች የማይሆንበት አንዱ ምክንያትም ይህ ነው።
ሌላው፡ በልጅነቴ ስለ አማርኛ የማልረሳው “ፍሰሃ” ተብሎ ስለሚጠራው ልጅ ስም ነበር። በሙሉ ማለት የሚቻል የኦሮሞ ተማሪ በትክክል መጥራት ከማይችላቸው ስሞች አንዱ ፍሰሃ ነበር። “ፍሰሃ” ን “ፊሳ” ነበር የምንለው። “ፊሳ /Fiissaa/” ቃሉ በኦሮምኛ ፍቺ ስላለው ለመጥራት አንቸገርም ነበር። “ፊሳ /Fiissaa/” በኦሮምኛ የሚያፏጭ ማለት ነው። አማርኛ ተናጋሪዎች እኛ “ፊሳ” ብለን ስንጠራ ይስቁብን ነበር። “ፊሳ” እያሉም ይተርቡን ነበር። ያኔ ፍሰሃን “ፍሰሃ” ብሎ እንደ አማርኛው አስተካክሎ መጥራት በአንዳንድ መምህራን ሳይቀር የእውቀት መለኪያ ተደርጎ የሚታይበት ዘመን ነበር። የማልረሳው ያልኩት ግን ፍሰሃን “ፍሰሃ” ብዬ ለማጥራት አንድ ቀን ያየሁት መከራ ነው። በዚያን ቀን ከትምህርት ቤት ወደ ቤት ገብቼ “ፍሰሃ” ን፡ ሞቼ ተሟሙቼ ተለማምጄ በሚቀጥለው ቀን አስተካክዬ ለማጥራት በመቃረቤ ተጨብጭቦልኝ ነበር። ሌሎችም የኔን አርአያ እንዲከተሉ ሲነገራቸው የተሰማኝ ኩራት ታላቅ ነበር። አማርኛን መውደድ ጀምሬም ነበር። ሆኖም እኔና አማርኛ ወድያው መልሰን ተቀያየምን ብቻ ሳይሆን ተጣላን። ፍቅራችን በአንድ አጋጣሚ ተበላሸ። ተቆራርተን ባንቀርም ጠጠር እንደ ገባው ጫማ እየቆረቆረኝ እስከመጨረሻው ዘለቅን። ለኔ የሚሆን ጥሩ የአማርኛ መምህርም ጣፋ። ጥሩዎች ቢኖሩም ለኔ ጥሩ አልነበሩም። ነገሩ የሆነው ሁለተኛ ክፍል ስማር ነበር። በዚህኛው ቀን ደግሞ መምህሩ በአማርኛ አረፍተነገር እንድሰራ ጠየቁኝ። እኔ ግን፡ እንኳን አረፍተነገር ልሰራ ቃሉንም አላውቀውም ነበር። መምህሩ በዘመኑ መምህራን ሞገስ ጥያቄውን ደገመልኝ። ያኔ፡ ለመምህር መልስ ሲሰጥ ቆሞ በመሆኑ ተነስቼ ቆምኩ። መልስ ግን አልነበረም። መምህሩ መልስ ጠብቆ ሲያጣ “ሰነፍ!” እያለ አከታትሎ አርጩሜውን አንጣጣብኝ። ያኔ የተገረፍኩት ዛሬም ያመኛል ብል ማጋነን ነው አትሉኝም። ከዚያ ቀን ጀምሮ አማርኛን ጠላሁት። እሱም ጠላኝ መሰለኝ ማትሪክ ላይ እንኳን ከኤፍ /መውደቂያ ውጤት/ ያመለጥኩት ለጥቂት ነበር። የ “ዲ /D/” ውጤት ካርዴ ላይ ሳይ ግን አልደነገጥኩም። ከኔና ከአማርኛ ዝምድና ሲመዘን በርግጥ ውጤቱ የሚያመረቃ ነበር። ይሁንና ከዚህ በፊት አማርኛን ምን ያህል እንዳስቸገርኩት አላውቅሁም። አሁንም ይኁው ማስቸገሬን አልተውኩም። በዚያ ላይ እናንተም “ድፈር” ብላችሁኛል። ይሄው ደፍሬያለሁ።
ወደ ቁም ነገራችን እንመለስ። የተነካካው የሳጥኑ ቁልፍ ላይ ነው ወደ ትዝታ ጎራ ያልነው። እንቀጥል።
በአንድ ወቅት፡ ተስፋዬ ገብረአብ፡ አበበ በለው ከሚባል የሬድዮ ጋዜጠኛ ጋር “የቡርቃ ዝምታ” መጽሃፍን በተመለከተ ቃለ-ምልልስ አድርጎ ነበር። በዚያ ቃለ-ምልልስ ላይ አበበ በለው “የቡርቃ ዝምታ” ኦሮሞንና አማራን የሚያጋጭ መጽሃፍ መሆኑንና በመጽሃፉ ላይ የተለያዩ ነጥቦችን ከተስፋዬ ጋር ካነሱ በኋላ ተስፋዬ መልሶ ጥያቄ ጠየቀው። ቃል በቃል የተስፋዬ ጥያቄ “አበበ በለው፡ ኦሮምኛን ታውቃለህ?” የሚል ነበር። የጋዜጠኛ አበበ መልስም አጭር ነበር። “አላውቅም!።” መለሰ ተስፋዬ። “ችግሩ ያ ነው።” ብሎ ነገረው። በተጨማሪም ቋንቋውን ችሎ፡ የኦሮሞ ህዝብ ውስጥ ዞሮ የኦሮሞን ህዝብ ስሜት የማዳመጥ እድል ቢያገኝ በ “የቡርቃ ዝምታ” እንደማይበረግግ በሚያውቀው አማርኛ ነገረው። ከዚህ የምንረዳው ሃበሾች ኦሮሞን ግፍ ፈጸሙበት እንጂ አያውቁትም። አዛውንቱ እንዳሉት፡ ተስፋዬ በኦሮሞ ህዝብ ላይ የደረሰውን ግፍ ነካካው እንጂ መች ነካው። እኔም “ተስፋዬ ገ/አብና የፓንዶራው ሳጥን” ብዬ ስጀምር፡ በዚህ አጭር መልእክት እነዚያ የተከመሩ ግፎችን ለመንካት አይደለም። ያ፡ ራሱን የቻለ ትልቅ ፕሮጀክት ነው። ቢሆንም የኦሮሞ ምሁራን ማለት እነ ፕሮፌሰር መሃመድ ሃሰን፡ እነ ፕሮፌሰር አባስ ሃጂ፡ እነ ፕሮፈሰር አሰፋ ጃለታ፡ ከዚህ ቀደም ይህንን የፓንዶራ ሳጥን ከፍተው ነካክተዋል። መጽሃፍ ሳይጽፉ ራሳቸው መጽሃፍ የሆኑ እንደነ ዶ/ር ገመቹ መገርሳ ሲነካኳቸው የፓንዶራውን ሳጥን ከፍተው ይነካሉ። ከውጭ ደግሞ፡ የጆን ማርከኪስ፡ እና የፕ/ር አስመሮም ለገሰ መጽሃፍት ስለ ፓንዶራው ሳጥን በጣም ግዙፍ የሆነ ግንዛቤ ይሰጣሉ። የኔ አነሳስ፡ ግን ተስፋዬ ስለ ኦሮሞ በመጻፉ ከሚደርስበት ውግዘትና ርግማን አኳያ የተሰማኝን ለማለት ፈልጌ እንጂ ትልቁን ሳጥን በዚህ አጭር ሃተታ ላነሳ ፈልጌ አይደለም። እንደዚያ ከተግባባን እንቀጥላለን። ከላይ እንዳልኩት ዛሬ አማርኛ የራሱ ያደረገኝ ሰው ባልሆንም መጥፎ የምባል አይደለሁም። በአማርኛ የሚጻፈውን ማንበብ የጀመርኩት በተስፋዬ ስራዎች ባይሆንም ዛሬ ስራዎቹ የበለጠ እንዳነብ አድርገውኛል። የሆነ ሆኖ “የተነካካው የሳጥኑ ቁልፍ” በተስፋዬ ብእር ቢነካካ ብዬ ተመኘሁ።
(ይቀጥላል)
——————————-
ክፍል ሁለት
እንደ መንደርደሪያ
“ተስፋዬ ገብረአብና የፓንዶራው ሳጥን”1 በሚል ርእስ የቀረበው ሃተታ የተለያዩ ተዛማጅ ጉዳዮችን የሚዳስስ ነው። የተለያዩ ይዘት ያላቸው ንኡስ ርእሶች አሉት። ኢትዮጵያ እንዴት እንደተመሰረተችና የአመሰራረት ታሪኳ ያልተዘጋ ስለመሆኑ፡ ከተመሰረተች በኋላ የማን እንደነበረች፡ ዛሬስ የማን እንደሆነችና ከዚህ በኋላስ የማን መሆን እንደሚገባት፡ አሁን ባለችበት የምትቀጥል ከሆነስ ምን ልትሆን እንደምትችል ያትታል። በአንዳንድ ወገኖች ዘንድ የኦሮሞ ስም ሲነሳ ለምን ቁጣ እንደሚቀሰቀስ የሚገነዘበውን ያካፍላል። ያለፈውን የማይተው ወገኖች ያለፈውን እንድንተው ለምን እንደሚመክሩንም ይጠይቃል። ኢትዮጵያዊ ለመሆን የግድ የህዝቦች ማንነት መጥፋት እንደሌለበት ያነሳል። በተጭማሪም የጽሁፉ ባለቤት ኢትዮጵያ የተባለችው አገር እንድትጠፋ አይመኝም። ይህ ግን ማንነቱን (ኦሮሞነቱን) ሳትሸራርፍ እስካከበረችለት ብቻ መሆኑን በጽኑ ያምናል። “ኢትዮጵያ አገሬ ለዘለአለም ትኖሪያለሽ!” የሚለው ምኞታዊ መፈክር ኢትዮጵያን ምሶሶና ማገር ሆኖ ያኖራታል ብሎ በፍጹም አያምንም። የህዝቦች የነጻነት ትግልም ያጠፋታል የሚል ፍራቻ የለውም። ከምኞታዊው መፈክርና ከተጨቋኞች የነጻነት ትግል ባሻገር ግን “ኦሮሚያ ነን ባዮች! ኦጋዴን ነን ባዮች! እከሌ ነን ባዮች! ወኔው ካላችሁ ተዋግታችሁ የልባችሁን ሙሉት!”2 የሚል የኢትዮጵያ አንድነት አቀንቃኞች ሰፈር መፈክር በጣም ያስፈራዋል። በአለማችን ፈሪ ወይም ጀግና ተብሎ የሚታወቅ ህዝብ የለም፡ ሁሉም ጋ ሁሉም አለና። ሿሚውና ሻሪው፡ የሁሉም ጌታ ጊዜ ነው። ተመሳሳይ አባባሎች ኤርትራ አገር እንድትሆን ትልቁን አስተዋጽኦ ያበረከቱ ስለመሆናቸው ቆመን አይተናል። ተመሳሳይ መፈክሮች ከቀጠሉ ነገም ሌላ ቀን የማይሆንበት ምክንያት አይታይም። እሱንም ቆመን እንድናይ፡ የዘመናችን ብቸኛ የአገር ወዳዶች መንገድ እያስተካከሉ ነው። ምኒልክ በህዝቦች ላይ ካደረሰው ወንጀልና በደል ይልቅ ዛሬ በአንድነት አቀንቃኞ ሰፈር የምናየው ንቀትና የታሪክ ክህደት ጩኀት ያንን አገር እንጦሮጦስ እያወረደው ነው። እና፡ በዚህ መጣጥፍ በአሁኑ ወቅት የትልቁ የኢትዮጵያ ችግር ትንንሽ አካላት ማለትም ለትልቁ ችግር ግብኣት እየሆኑ ያሉት (ከላይ ያነሳሁት አይነት አባባሎች) ይነሳሉ። “የኤርትሪያውያን ሳቅ” የሚል አጭር ሃተታም በመጣጥፉ ተካቷል። በመጨረሻም፡ የኦሮሞን ስም በጥበበኛው ብእሩ በበጎ በማንሳቱ ሲወገዝ የኖረና “ከጠላቶቿ ጋር ኢትዮጵያን ሊያጠፋ ያበረ” ተብሎ ሲረገም ስለቆየውና እየተረገመ ስላለው ደራሲ ተስፋዬ ገብረአብ “ተስፋዬ ገብረአብና የፓንዶራው ሳጥን “ በሚለው ሃተታ እናሳርጋለን። ስንጀምር ግን፡ “የአለማችንን ምርጡን ቋንቋ የተማርኩት ከእናቴ ነው” በሚል ርእስ ነው፡ ተከታተሉኝ።
“የአለማችንን ምርጡን ቋንቋ የተማርኩት ከእናቴ ነው”
በመግቢያው ለመነካካት እንደተሞከረው፡ በኢትዮጵያ የሚኖሩ አማርኛ ተናጋሪ ያልሆኑ ህዝቦች ባለፉበት የዘመናት ሂደት በአማርኛ ቋንቋ የደረሰባቸው በደል ቀላል አልነበረም። ይህን ስንል ግን በምንም ይሁን በምን የተማሩት የአማርኛ ቋንቋ በፍጹም አልጠቀማቸውም ማለት አይደለም። ቋንቋ መሳሪያ ነውና ህዝቦች ይጠቀሙበታል። ይግባቡበታል። በተጨማሪም የሌሎችን ህዝቦች ቋንቋ ለማይናገሩ የአማርኛ ቋንቋ ተናጋሪዎች መልእክቶቻቸውን ማስተላለፍ በመቻላቸው መልእክቶቻቸውን ማስተላለፍ ከማይችሉት ይሻላሉ ብዬ አምናለሁ። ነገር ግን፡ ከአማርኛ በስተቀር ሌሎች የአገሪቱን ቋንቋዎች የማይችሉ፡ የገዢዎች መዘምራን የነበሩና ዛሬም ለዚያው የሚታገሉ ወገኖች ሌሎች በአገሪቱ የሚነገሩ ቋንቋዎችን አለማወቃቸው የጠቀማቸው አይመስለኝም። ምክኒያቱም አማርኛን ለማያውቁ የዚያ አገር ህዝቦች መልእክቶቻቸውን ሊያስተላልፉ አይችሉም ነበርና። ያ ችግር ዛሬም አብሯቸው አለ። የተቀየረው ዘመን ብዙ ነገሮችን የቀየረ ከመሆኑ አንጻር ደግሞ ችግሩን የበለጠ አክብዶታል። በሌላ በኩል ማንኛውንም ቋንቋ ማወቅ አይጠቅምም ይሆናል። እንደማይጎዳ ግን አፌን ሞልቼ መናገር እችላለሁ። የሚጎዳ ከሆነ ግን (በኛው አገር ሲሆን እንደነበረው) ህዝቦች ህግ ፊት ቀርበው፡ በማያውቁት ቋንቋ ተዳኝተው ፍትህ ሲያጡ ነው። ያ ቋንቋ ሌሎችን ቋንቋዎች ለማጥፋት ከሰራ ነው። ህዝቦች በሚችሉት ቋንቋ ትክክለኛ ስሜታቸውን እንዳይገልጹ የስነልቦና ጫና በመፍጠር ጭምር በአደባባይ እንዳይነገር መከልከል ነው። ደራሲ ተስፋዬ ገብረአብ “የስደተኛው ማስታወሻ” በሚል ርእስ ባሳተመው መጽሃፉ፡ “ጫልቱ እንደ ሄለን” በሚለው ንኡስ ርእስ፡ በዚያ አገር ይደርሱ የነበሩ በደሎችን በጫልቱ ሚዳክሳ (Caaltuu Midhaksaa) በኩል በተባ ብእሩ አስነብቦናል። ጫልቱ ላይ የደረሰው መከራ (የቋንቋን ተጽእኖ ጨምሮ ማለት ነው) እስከ ህይውቷ ፍጻሜ የተከተላት ነበር። የዚህ ጽሁፍ ጸሃፊ ከላይ በመግቢያው ካነሳው ሌላ “የጫልቱ ሚደክሳን ያህል ከባድ አይደለም” ሊባል የሚችል ሌላም (የአማርኛ ቋንቋ ተጽእኖ) ገጠመኝ ነበረው። ገጠመኙ የቋንቋን ተጽእኖ የሚያሳይ ሲሆን የሆነው በደርግ ዘመን ነበር። ልጁ በ6 አመቱ ት/ቤት አንደኛ ክፍል ይገባል። እንደሚታወቀው በዘመኑ ተማሪዎች ክፍል ውስጥ ስማቸው የሚጠራው በቁጥር ነበር። በመጀመሪያ ትምህርት ከመጀመራቸው በፊት የሚጠሩበት ቁጥር በአማርኛ ይነገራቸዋል። በክፍል ውስጥ ወደ 87 ከሚሆን ተማሪ የዚህ ልጅ የክፍል ቁጥር 34 ነበር። አማርኛን የማያውቀው ይህ ልጅ “34 ቁጥሩ” ከነ አራት፡ አስራ አራት፡አርባ አራት፡ ሃምሳ አራት ወዘተ ጋር ተምታቶበት ሲጠራ “አቤት” ሳይል ይቀራል። መምህሩ ለአራት ቀናት በቁጥሩ ጠርተው ሲያጡት በአምስተኛው ቀን በስሙ ለመጥራት ይሞክራሉ። የሚገርመው ስሙም ሲጠራ ተደናገረ። ስሙ “ጉተማ /Gutama/” ነበር። እሱንም ቀይረው “ከተማ” ብለው የበለጠ አደናገሩት። እናም “ከተማ” ተብሎ ሲጠራ ስሙ ስላልሆነ ዝም አለ። መምህሩ ለአራት ቀናት የት እንደነበረ ብቻ ሳይሆን ሲጠራ ለምን “አቤት” እንዳላለ በማያውቀው አማርኛ ያምባርቁበታል። መልስ አልነበረም። አፉን በፈታበት ቋንቋ ቁጥር መለየት የማይችል ልጅ አልነበረም። በሚያውቀው ቋንቋ ቢጠየቅ “ስሜ ከተማ ሳይሆን ጉተማ ነው” ብሎ መመለስ የማይችል ልጅም አልነበረም። በማያውቀው ቋንቋ የተጠየቀውን ባለመመለሱ ግን ተገረፈ። አልቅሶም ዝም ይላል። በኋላም 34 ቁጥሩን ጠብቆ አቤት እንዲል አሁንም በዚያው በአማርኛ ከማስጠንቀቂያ ጋር ይነገረዋል። ያች የተረገመችዋ 34 ቁጥር ከዚያ በኋላም ማምታታቷ አልቀረም። ልጁ ግን እነኛን አራቶች መለየት ባይችልም በሚቀጥለው ቀን ላለመገረፍ በልጅነት አእምሮው መላ ዘየደ። አራትና የአራት ዘሮችን (አራትን፡ አስራአራትን፡ ሃያአራትን፡ አርባአራትን፡ ሃምሳአራትን…) በሙሉ ጠብቆ አቤት ሊል ወሰነ። በመሃል ያች መዘዘኛዋን ቁጥር አግኝቶ ከመመታት ይድናልና። ለሶስት ቀናት ችግሩን በዚያዉ ዘዴ ከተወጣ በኋላ በአራተኛው ቀን ተያዘ። “ይሄ ልጅ ሁሉንም ቁጥር አቤት ይላል” ብለው አማርኛ ተናጋሪ ልጆች ጠቆሙት። ዛሬም ግርፍ ሆነ። በቃ! የዚያ ልጅ የትምህርት አለም እዚያ ላይ አከተመ። ልጁ ወደ ት/ቤት እንዲመለስ በቤተሰብ ቢገደድም አሻፈረኝ አለ። ወደ /ቤት እንዲመለስ በቤተሰብ የተገረፈው ግርፍ ምናልባትም ት/ቤት ከተገረፈው ይበልጥ ነበር፡ አልተሳካም እንጂ። በርግጥ ነገሩ የሚያስቅና ቀላል ሊመስል የሚችል ነው። ነገር ግን ቢማር፡ ቢያንስ በኑሮው የተሻለ ሰው ይሆን ይችል የነበረ ልጅ የማያውቀው ቋንቋ ባደረሰበት ተጽእኖ በምናውቃት አገር /ኢትዮጵያ/ አፈር ገፊ /ገበሬ/ ሆኖ ቀረ። (ልጁ የዚህ ጽሁፍ ጸሃፊ ወንድም ነው። ሁነቱ አሳዛኝ ቢሆንም ዛሬም ድረስ በቤተሰብ ውስጥ ከትውስታ መሳቂያዎች አንዱ ነው።) የህዝቦችን ህይወት ያበላሹ፡ ከዚህና ከ “ጫልቱ እንደ ሄለን” የከፉትን ብዙ ማንሳት ይቻላል። ተስፋዬ ገብረአብ ከፓንዶራው ሳጥን ግፎች አንዷን ሰበዝ መዞ፡ከላይ ያነሳሁትን ማለት ”ጫልቱ እንደ ሄለን” ን አቅርቦልን ነበር። ይህ ጸሃፊም፡ በዚህ አጋጣሚ፡ “የስካር መንፈሱ ፊርማ” በሚል ርእስ አንዷን ከፓንዶራው ሳጥን መዞ ወደፊት ሊያቀርብላችሁ ቃል ይገባል።
በሌላ በኩል፡ ማንኛውም የሰው ልጅ ከየትኛውም ቋንቋ በላይ የሚመቸው አፉን የፈታበት ቋንቋ ነው። አፉን የፈታበት ቋንቋ ከምንም ይበልጥበታል። ይህን ስንል ግን ሌላውን ቋንቋ ይጠላል ማለት አይደለም። ነገር ግን በኛ አገር አማርኛ ተናጋሪ ያልሆኑ ህዝቦች አማርኛን ትተው የእናት አባቶቻቸውን ቋንቋ ሲጠቀሙ፡ በአማርኛ ቋንቋ ጥላቻነት ይፈረጃል። አንዳንዴ፡ በጠባብነትም ያስፈርጃል። በርግጥ ህዝቦች አፋቸውን ባልፈቱበት የአማርኛ ቋንቋ ትክክለኛ ስሜታቸውን ማስተላለፍ ሳይችሉ ሲቀሩ “ተብታባ” እየተባሉ ሲሰደቡ መኖራቸውና በአማርኛ ሌሎችን ቋንቋዎች ለማጥፋት ሲሰራ የኖረው በደል በቋንቋው ላይ የራሱን ተጽዕኖ ማሳረፉ ባይቀርም ህዝቦች የእናት አባቶቻቸውን ቋንቋ አጥብቀው የሚፈልጉት ግን የአማርኛን ቋንቋ ስለሚጠሉ አይደለም። እውነተኛ ስሜታቸውን መግለጽ የሚችሉት አፋቸውን በፈቱበት ቋንቋ በመሆኑ እንጂ። ልጅት ነበረች አሉ፡ በአንድ ወቅት። “የአለሙን ምርጥ ቋንቋ የተማርሽው ከማነው?” ስትባል “የአለማችንን ምርጡን ቋንቋ የተማርኩት ከእናቴ ነው” አለች ይባላል። በሚቀጥለው ክፍል ሶስት “ከትክክል በላይ የሆነ አባባል” በሚል ርእስ እንገናኛለን።
አማን ሄደቶ ቄረንሶ ነኝ።
ቻው!
Nagayaan naaf turaa!
1. የ “ፓንዶራ ሳጥን” ትርጉሙ ሰፋ ያለ ቢሆንም፡ ስናሳጥረው ፡አስቀያሚ ነገሮችን አጭቆ የያዘ እቃ ምሳሌ ነው። በዚህ ሃተታ ደግሞ የፓንዶራ ሳጥን የሚወክለው ኢትዮጵያን ነው።
2. “ኦሮሚያ ነን ባዮች … የሰላዮች ትንቅንቅ” መጽሃፍ፡ ደራሲው ንጋቱ ክፍሌ፡ እ.ኢ.አ. ነሃሴ፡ 1998.

No comments:

Post a Comment